No Ethnic ID cards in Addis Abeba – የጎሳ መታወቂያ ተከለከለ::

የአዲስ አበባ ነዋሪዎች መታወቂያ መመርያ ተሻሻለ

29 August 2018 ውድነህ ዘነበ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የነዋሪዎች ምዝገባና የመታወቂያ አሰጣጥ መመርያ ቁጥር 3/2010 በማሻሻል፣ ብሔር የማይጠቀስበት መታወቂያ ለነዋሪዎች መስጠት ሊጀምር ነው፡፡

የተሻሻለው መመርያ የከተማውን ነዋሪዎች የመታወቂያ አሰጣጥ ከማነዋል ወደ ዲጂታል የሚያሸጋግርና በአሻራ የተደገፈም ስለሚሆን፣ በሐሰተኛ ሰነድ መታወቂያ የያዙ ግለሰቦችን መለየት ያስችላል ተብሏል፡፡

ይህንን አሠራር ተግባራዊ ለማድረግ በክፍላተ ከተሞችና በወረዳዎች የሚገኙ አመራሮችና ሠራተኞችን ያካተተ ሥልጠና፣ ቅዳሜ ነሐሴ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ተሰጥቷል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች መታወቂያ ብሔርን የሚጠቅስ በመሆኑ፣ ይህም ከአንድነት ይልቅ ልዩነቶችን የሚያጎላ ስለሆነ በተገኘው አጋጣሚ ቅሬታ ሲቀርብበት ቆይቷል፡፡

ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ሥልጣን በያዙ ማግሥት ይህንን ጉዳይ በሚመለከት እንደገለጹት፣ የመታወቂያ ጉዳይ ቀላል ቢመስልም ከፍተኛ ቅሬታ እየተነሳበት በመሆኑ አሰጣጡን ማስተካከል ይገባል፡፡

በዚህ መሠረት መመርያው የተሻሻለ በመሆኑ በመታወቂያ አሰጣጥ ላይ በሁለት መሠረታዊ ጉዳዮች ለውጥ ያመጣል ተብሏል፡፡

የመጀመሪያው በመታወቂያ ላይ ከብሔር ስያሜ ይልቅ ኢትዮጵያዊ ሲባል፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ አሰጣጡ ዲጂታል ስለሚሆን ሕገወጦችን መለየት እንደሚያስችል ተገልጿል፡፡ በተለይ ሕገወጥ ጥቅም የሚሹ ግለሰቦች፣ በተለያዩ ዘዴዎች መታወቂያ በማውጣት ሲያገኙ የቆዩትን ጥቅም እንደሚያስቀር ታምኗል፡፡

ለአብነት በክልል ከተሞች የግል መኖሪያ ቤት እያላቸው በሕገወጥ መንገድ  የአዲስ አበባ ነዋሪነት መታወቂያ በመያዝ ኮንዶሚኒየም ቤት የተቀራመቱትን ዕርምጃ መውሰድ ያስችላል ተብሏል፡፡

የተሻሻለው መመርያ የኮምፒዩተር አመዘጋገብ፣ የነዋሪዎች ምዝገባ ሒደት፣ የነዋሪዎች መታወቂያ ይዘትና የመሸኛ ጉዳይን በዝርዝር ይዟል ተብሏል፡፡

Recommended For You

About the Author: admin